የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ከኤስ ኦ ኤስ ሄርማን ገማይነር ትምህርት ቤት- ሀዋሳ ጋር ለመስራት የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረመ።
ጥር 18/2015 ዓ.ም በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ልዩ ችሎታ ያላቸውን ተማሪዎች ከኤስ ኦ ኤስ ሄርማን ገማይነር ሃዋሳ ትምህርት ቤት ተቀብሎ በኢንስቲትዩውቱ በሚገኘው ቴክኖሎጂ ቢዝነስ ኢንኩቤሽን ማዕከል ለማሰልጠን የመግባቢያ ሰነድ ተፈራረመ፡፡
የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ዶ/ር ፋሲካ ቤተ እንደተናገሩት በዚህ ስምምነት መሰረት ጎበዝ፣ ልዩ ችሎታና ተሰጥኦ ያላቸው ታዳጊ ተማሪዎች ወደ ማዕከላችን ገብተው ከንድፈ ሃሳብ በዘለለ በተግባር ፈጠራዎቻቸውን እንዲያሳድጉ ስልጠና የሚያገኙበት፣ ሃሳቦቻቸውን የሚተገብሩበት እንዲሁም የተለያዩ የቴክኖሎጂ ሽግግር ውጤቶችን የማበልፀግ ዕድሉን የሚያገኙበት በመሆኑ ልጆች ከሚማሩበት ትምህርት ቤት ውጪ በዩኒቨርሲቲው የዚህ መሰሉን ዕድል ማግኘት መነሳሳትን የሚፈጥርላቸው መሆኑን በመግለፅ የነገው ሀገር ተረካቢ ትውልድ እንደመሆናቸው ያላቸውን ችሎታ ቀድመው እንዲለዩም ከወዲሁ መሰረት ለማስያዝ ጉልህ ሚና እንዳለው ተናግረዋል፡፡
የኤስ ኦ ኤስ ትምህርት ቤት ስራ አስኪያጅ አቶ አለሙ ተሰማ በበኩላቸው ከሳይንስና ፈጠራ ስራዎች ጋር በተያያዘ ህብረት ፈጥሮ እና ተቆራኝቶ መስራት በጣም አስፈላጊና ሃገርን የሚቀይር አካሄድ መሆኑን ገልፀው ልጆች ላይ ከወዲሁ መዋዕለ ነዋይንም ሆነ አስፈላጊውን ነገር ማፍሰስ ትውልድን ለመቅረፅ ጠቀሜታው የበዛ በመሆኑ ዩኒቨርሲቲው ተማሪዎቹ ሃሳባቸውን የሚያጎለብቱበትን መንገድ በማመቻቸቱ ምስጋናችን የላቀ ነው ብለዋል፡፡