የአዋዳ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ በአዲሱ የ2015ዓ.ም ዕቅድ ላይ ውይይት አካሄደ።
በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የአዋዳ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ በተከለሰው የ2015ዓ.ም ዕቅድ ላይ ከኮሌጁ ኃላፊዎች፣ መምህራን እና የአስተዳደር ሰራተኞች ጋር ህዳር 27 ቀን 2015 ዓ.ም ውይይትና ምክክር አካሂዷል፡፡
የአዋዳ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጅ ዲን ዶ/ር ወገኔ ማርቆስ ኮሌጁ የተሰጡትን የመማር ማስተማር፣ የምርምርና የማህበረሰብ አገልግሎት ስራዎች ለማከናወን እንደወትሮው ሁሉ የአስር ዓመት መሪ ዕቅድና የ2015 ዓ.ም ዕቅድ በማዘጋጀት ወደ ተግባር የገባ ቢሆንም ከትምህርት ሚኒስቴር በተቀመጠው አቅጣጫ መሰረት ዩኒቨርሲቲው ያዘጋጀውን ዕቅድ መሰረት በማድረግ በኮሌጅ ደረጃ ተከልሶ የተዘጋጀውን ዕቅድ ሁሉም መምህራን እና የአስተዳደር ሰራተኞች እንዲወያዩበት የተዘጋጀ መድረክ ነው ብለዋል፡፡
ዲኑ አክለውም ባለፉት ወራቶች የተከናወኑ ተግባራትንና በዚህ ዕቅድ መሰረት የሚተገበሩ ተግባራትን ውጤታማ ለማድረግ ዕቅድን መረዳት አስፈላጊ በመሆኑ ሁሉም በሚቀርበው ሰነድ ላይ ተወያይቶ በባለቤትነት የሚመለከቱትን የስራ ድርሻዎች በመውሰድ እንዲተገብር አደራ ያሉ ሲሆን የተከናወኑ ተግባራትም በቀጣይ በሪፖርት እንዲቀርቡ በአግባቡ መሰነድ እንዳለባቸው ተናግረዋል፡፡
በፕሮግራሙም ላይ የኮሌጁ የ2015 በጀት ዓመት የተከለሰ ዕቅድ ዝርዝር ተግባራት ቀርቦና ውይይት ተካሂዶበት ፕሮግራሙ ተጠናቋል፡፡