የትምህርት ኮሌጅ ለተመራቂ ተማሪዎች በመውጫ ፈተና ዙሪያ የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና አዘጋጀ።
በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የትምህርት ኮሌጅ ለተመራቂ ተማሪዎች በመውጫ ፈተና ዙሪያ ህዳር 22 ቀን 2015 ዓ.ም የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና ሰጥቷል።
የትምህርት ኮሌጅ የዕቅድና መረጃ አስተዳደር አስተባባሪአቶ ገላን ጋጉራ ሲገልጹ በሀገራችን የትምህርት ስርዓትን ለማሻሻል እና ጥራትን ለማሳደግ ጥራት ላይ ትኩረት ተሰጥቶ እየተሰራ እንደሆነ ገልፀዉ የከፍተኛ ትምህርት የመዉጫ ፈተና አፈፃፀም መመሪያን በተመለከተ ለመምህራኖች ግንዛቤ የተሰጠ ሲሆን በዚህ ፕሮግራምም በመዉጫ ፈተና ምንነትና አፈፃፀም ላይ፣ ከተማሪዎች ምን ይጠበቃል፣ በዕቅድ መመራትና ተግባራዊ ማድረግ ላይ፣ በጋራ ማንበብና እርስ በእርስ መጠያየቅ፣ ማጠናከሪያ ትምህርቶችና ሞዴል ፈተናዎች ላይ ትኩረት ማድረግ ዙሪያ ለተማሪዎች የግንዛቤ ማስጨበጫ ስልጠና እየተሰጠ ይገኛል ብለዋል።
በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የሳይኮሎጂ ትምህርት ክፍል መምህር ዕጩ ዶ/ር ሀብተማርያም ካሳ ተማሪዎች ፈተናን በተመለከተ ራሳቸዉን እንዴት በእዉቀት፣ በስነልቦና እና በአካል ማዘጋጀት እንዳለባቸዉ ያስተማሩ ሲሆን ተማሪዎችም በተነሱት ነጥቦች ላይ ያልገባቸዉን እና ተጨማሪ ገለፃ በሚፈልጉት ነጥቦች ላይ ጥያቄዎችን አንስተዉ ከመድረኩም ምላሽ ተሰጥቶባቸዉ ፕሮግራሙ ተጠናቋል።