በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የተፈጥሮና ኮምፕቴሽናል (ቀመር) ሳይንስ ኮሌጅ ለድህረ ምረቃ መምህራኖች በበይነ መረብ ስብሰባዎችን ለማካሄድ በሚያስችሉ የሶፍትዌር አማራጮች ላይ ህዳር 21 ቀን 2015 ዓ.ም ስልጠና ሰጥቷል።
የተፈጥሮና ኮምፕቴሽናል ሳይንስ ዲን ዶ/ር ዙፋን በደዊ በስልጠናዉ መክፈቻ ላይ ይህ ስልጠና የሶፍትዌር አማራጮችን በመጠቀም መምህራኖቻችንን ስብሰባ ከማድረግ በዘለለ የተለያዩ የምርምር ዉጤቶችን እና ሳይንሳዊ ግኝቶችን በወቅቱ እንዲለዋወጡ፣ አዉደ ጥናቶችንና ጉባኤዎችን እንዲያዘጋጁና እንዲካፈሉ የሚረዳ በመሆኑ የጊዜና የገንዘብ ብክነትንም የሚያስቀር ነው ብለዋል። የኮሌጁ ዲን አክለውም መምህራኖቻችን የቴክኖሎጂዉ ዉጤት ያመጣላቸዉን ትሩፋቶች በመላመድና በመጠቀም ባሉበት ሆነዉ ጊዜና ቦታ ሳይገድባቸዉ እነዚህ ሶፍትዌሮችን ለአካዳሚክ ጉዳዮች ሊገለገሉበት ይገባል ብለዋል።
የተፈጥሮና ኮምፕቴሽናል ሳይንስ ኮሌጅ ድህረ ምረቃ አስተባባሪ ዶ/ር ያደሳ ጎንፋ መምህራኖቻችን በዚህ ስልጠና ያገኙትን እዉቀትና ክህሎት በመጠቀም በተለይ የድህረ ምረቃ ተማሪዎች የሚሰሯቸዉን የመመረቂያ ፅሁፎች ካሉበት ሆነዉ ለመገምገምና ለማማከር እንዲሁም እርምቶችን ለመስጠት እንዲሁም በጋራ የሚሰሩ ፕሮጀክቶችን በሀገር ዉስጥና ዉጪ ካሉ ባለድርሻና አጋር አካላት ጋር በጋራ ለመመካከር ይረዳቸዋል ብለዋል።
የአይ ኤስ ቲ ዳይሬክቶሬት የመሰረተ ልማት ቡድን መሪ አቶ ሙሉጌታ ተስፋዬ ስልጠናዉ በጎግል የመሰብሰቢያ(Google meeting) ሶፍትዌር ላይ ያተኮረ ሲሆን ከጎግል ድርጅት ጋርም ዩኒቨርሲቲዉ ባለዉ መልካም ግንኙነት በነፃ እንዲጠቀም ከተፈቀዱለት አማራጮች አንዱ መሆኑን ገልፀዉ መምህራኖችም ባሉበት ሆነዉ ተማሪዎቻቸዉን ለማማከር፣ ለመገምገምና ለመመዘን የሚረዳቸዉ መሆኑን ገልፀዋል።
እንዲሁም የተለያዩ ስብሰባዎችንና ጉባዔዎችን ለማድረግም ይረዳል ብለዋል።