በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ስር በ2014ዓ.ም የተሰሩ የማህበረሰብ አገልግሎት የምርምር ፕሮጀክቶችን ለመገምገም በሰኔ 11 ቀን 2014 ዓ.ም ዓመታዊ ወርክሾፕ አካሄደ፡፡
የማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ማርቆስ ፍስሃ የዚህ ወርክሾፕ ዓላማ በዓመቱ በማህበረሰብ አገልግሎት ዳይሬክቶሬት ስር የተሰሩ የማህበረሰብ አገልግሎት ፕሮጀክቶችን ለመገምገም ሲሆን ፕሮጀክቶቹ በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ምርምር ፕሮግራም ተለይተው ትኩረት በተሰጠባቸው በግብርና፣ በእንስሳት ዕርባታ፣ በአካባቢ ጥበቃ፣ በትምህርት፣ በጤናና ስነ-ምግብ እንዲሁም በሌሎች ማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ ትኩረት በማድረግ የማህበረሰቡን ችግር የሚፈቱ መሆናቸውን ተናግረዋል፡፡
ዳይሬክተሩ አክለውም በወርክሾፑ 11 የማህበረሰብ አገልግሎት ፕሮጀክቶች ማለትም አምስት ከግብርና ኮሌጅ፣ ሶስት ከህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ፣ አንድ ከተፈጥሮና ቀመር ሳይንስ ኮሌጅ፣ አንድ ከወንዶ ገነት ደንና ተፈጥሮ ሀብት ኮሌጅ እና አንድ ከሕግና ገቨርናነስ ኮሌጅ ቀርበው እየተገመገሙ መሆናቸውን እና በዋናነትም በ2014ዓ.ም የተገኙስኬቶችን፣ ልምዶችን እና ያጋጠሙ ችግሮች ላይ ግምገማ በማድረግ ሌሎችም ከዚህ ተሞክሮ በመቅሰም ዩኒቨርሲቲው ካስቀመጠው አቅጣጫ ጋር በማጣጣም የራሳቸውን ፕሮጀክቶች እንዴት ማስኬድ እንዳለባቸው የምክክርና የልምድ ልውውጥ የሚያገኙበት መሆኑን ገልፀዋል፡፡