የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት እኔ የእህቴ ጠባቂ ነኝ በሚል መሪ ቃል ዓለም አቀፍ የሴቶችን ቀን አከበረ፡፡
በዓለም ለ111ኛ ጊዜ በሀገራችን ደግሞ ለ46ኛ ጊዜ የሚከበረውን ዓለም አቀፍ የሴቶች ቀንን አስመልክቶ በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት እኔ የእህቴ ጠባቂ ነኝ በሚል መሪ ቃል ዓለም አቀፍ የሴቶችን ቀን መጋቢት 7 ቀን 2014 ዓ.ም አከብሯል፡፡
በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ሳይንቲፊክ ዳይሬክተር ዶ/ር ኢንጂነር ፋሲካ ቤተ በዚሁ ወቅት ባደረጉት የመክፈቻ ንግግር የበዓሉ ዋና ዓላማ በሴቶች ላይ ለዘመናት ሲደረግ የነበረውን ፆታዊ አድሎን በማስቀረት ሴቶች ልክ እንደወንዶች ሁሉ በማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊ እና ፖለቲካዊ እንቅስቃሴዎች እንዲሳተፉ በማስቻል በስራ ቅጥር፣ በትምህርት ዕድል እና በፍትሃዊ የሀብት ክፍፍል ተጠቃሚ እና ውጤታማ እንዲሆኑ ከሁላችንም ምን ይጠበቃል የሚለውን ለመወያየት እና አቅጣጫ ለማስያዝ መሆኑን ገልፀው ከቅርብ ጊዜ ወዲህ በዩኒቨርሲቲያችን የሴት መመህራኖቻችን ቅጥር እና ተማሪዎቻችን ቅበላ ቁጥር እየጨመረ የመጣ ቢሆንም በቀጣይ በርካታ ስራዎች ይጠብቁናል ብለዋል፡፡
በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የሴቶች ህፃናት ወጣቶችና ኤች. አይ. ቪ ኤድስ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ወ/ሮ ምህረት ገነነ ዕለቱን አስመልክቶ እንደተናገሩት ሴቶች ለዘመናት የሚደርስባቸውን ጫና በመታገል ከወንዶች እኩል እና ፍትሃዊ በሆነ መልኩ የመቀጠር፣ የላባቸውን ዋጋ የማግኘት፣ የስራ ሰዓት መከበር እንዲሁም በማህበረሰቡ ውስጥ ያለባቸውን በርካታ ውስብስብ ችግሮችን ለማስበገድና ለመብታቸው የታገሉበትን ቀን አስመልክቶ የሚከበር ቀን መሆኑን አውስተው ዳይሬክቶሬቱ የተለያዩ የአሰራር ስርዓቶችን በመዘርጋት ሴት ተማሪዎችን፣ ሰራተኞችን እና መምህራንን እየደገፈ እና በተለያዩ ክበቦች አማካኝነትም የተለያዩ የበጎ አድራጎት እንቅስቃሴዎችን እያደረገ እንደሆነ ገልፀዋል፡፡
በዕለቱ በዩኒቨርሲቲው የተመሰረተው መቅረዛዊያን የተማሪዎች ክበብ የተለያዩ ጭውውቶችን አቅርበው ታዳሚውን ያዝናኑ ሲሆን በኢንስቲትዩቱ በትምህርት ክፍላቸው የላቀ ውጤት ላስመዘገቡ ሴት ተማሪዎች የማበረታቻ ሽልማት ተደርጎላቸው ፕሮግራሙ ተጠናቋል፡፡