የምርምር ፕሮግራሞች ዳይሬክቶሬት ለመምህራን እና ወጣት ተመራማሪዎች ስልጠና ሰጠ፡፡
በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ም/ፕሬዚዳንት ጽ/ቤት ስር የሚገኘው የምርምር ፕሮግራሞች ዳይሬክቶሬት ለመምህራን እና ወጣት ተመራማሪዎች በምርምር ምክረ-ሃሳብ እና ሪፖርት አፃፃፍ ላይ ከየካቲት 10/2014ዓ.ም ጀምሮ ለሁለት ቀናት ስልጠና እየሰጠ ይገኛል፡፡
የምርምርና ቴክኖሎጂ ሽግግር ም/ፕሬዚዳንት ዶ/ር ታፈሰ ማቲዎስ ስልጠናውን ሲከፍቱ ዩኒቨርሲቲው ላለፉት 46 ዓመታት በርካታ ችግር ፈቺ ምርምሮችን በማድረግ የራሱን አስተዋፅኦ ሲያደርግ የቆየ ሲሆን ካለፈው ዓመት ጀምሮ ደግሞ ዩኒቨርሲቲያችን በሀገራችን የምርምር ዩኒቨርሲቲ ተብለው ከተለዩ ስምንት ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ እንደመሆኑ እና ከዚህ በፊት ሁለት የነበሩት የምርምር ጆርናሎች ወደ ስምንት ከፍ በመደረጋቸው ተመራማሪዎች ጥራት ያላቸው እና ደረጃቸውን የጠበቁ የምርምር ውጤቶችን ለማሳተም እንዲረዳቸው የመምህራንን እና ተመራማሪዎችን አቅም ለማጎልበት ታስቦ የተዘጋጀ በመሆኑ የዚህ መሰሉ ስልጠና ሚናው የጎላ ነው ብለዋል፡፡
የምርምር ፕሮግራሞች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ራህመቶ አበበ በተደረገው ጥናት ውጤት መሰረት በዩኒቨርሲቲው የምርምር ጥናት ውጤቶች ውድድር ለማድረግ ታስቦ የሚቀርቡት ወረቀቶች የጥራት ደረጃቸውን የጠበቁ ባለመሆናቸው የሚታዩትን ክፍተቶች ለመሙላት ታስቦ እና ዩኒቨርሲቲው በሁለት ዓመት ጊዜ ውስጥ የዩኒቨርሲቲው መምህራን እያንዳንዳቸው ቢያንስ አንድ የምርምር ውጤት ታዋቂ በሆኑ ጆርናሎች ማሳተም እንዳለባቸው አቅጣጫ በማስቀመጡ ወደፊት ይሄንን ተፈፃሚ ለማድ ግና ለመደገፍም ይረዳል ብለዋል፡፡ ዶ/ር ራህመቶ አክለውም ይህ ስልጠና ከዚህ በፊት ከማህበራዊና ስነ-ሰብ፣ ህግና ገቨርናንስ፣ ትምህርት፣ ቢዝነስና ኢኮኖሚክስ ኮሌጆች እና ከዳዬ ካምፓስ ለተመረጡ 50 መምህራን የተሰጠ ሲሆን አሁን ደግሞ ከተፈጥሮና ቀመር ሳይንስ፣ ግብርና፣ ህክምናና ጤና ሳይንስ፣ ወንዶ ገነት ደ/ተ/ሃብት ኮሌጆች እና ከቴክኖሎጂ ኢንስቲትዩት ለተመረጡ 50 መምህራን ስልጠና እየተሰጠ እንደሚገኝ ገልፀው በቀጣይም በምርምር ዘዴና በሶፍትዌር የታገዘ ዳታ ትንተና ላይ እንዲሁም የምርምር ውጤቶችን በታዋቂ የምርምር ጆርናሎች ላይ እንዴት ማሳተም እንደሚቻል ስልጠና ይሰጣል ብለዋል፡፡