የህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ 360 ተማሪዎችን አስመረቀ።
የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ህክምናና ጤና ሳይንስ ኮሌጅ ለ15ኛ ጊዜ 320 የጤና ሳይንስ ተማሪዎችንና ለ6ኛ ጊዜ ደግሞ 40 ስፔሻልስት ሐኪሞችን ጥር 14 ቀን 2014 ዓ.ም አስመርቋል:: ከተመራቂዎቹም መካከል 246 ተማሪዎች በመጀመሪያ ዲግሪ፣ 74 ደግሞ በሁለተኛ ዲግሪ በተለያዩ የጤና ሳይንስ ዘርፎች ትምህርታቸውን ሲከታተሉ የቆዩ ሲሆን 40 የሚሆኑት ተመራቂ ሐኪሞች በስፔሻሊቲ ሕክምና የሰለጠኑ መሆናቸው ታውቋል፡፡
ዶ/ር አያኖ በራሶ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዩኒቨርሲቲው በምስራቅ አፍሪካ ከሚገኙ 10 ምርጥ ዩኒቨርሲቲዎች አንዱ የመሆን ራዕይ አንግቦ አዲስ ስትራቴጂክ ዕቅድ ቀርጾ በመስራት ላይ የሚገኝ ሲሆን በተመረጡ የትኩረት መስኮችና የልህቀት ማዕከላት ልዩ ትኩረት ሰጥቶ እየሠራ እንደሚገኝ ገልፀዋል፡፡ ዩኒቨርሲቲው በ2013 የትምህርት ዘመን በሁሉም የትምህርት መረሃ ግብሮች ከ40 ሺ በላይ ተማሪዎችን በመደበኛና በተከታታይ ትምህርት በሰባት ካምፓሶች እያስተማረ የቆየ ቢሆንም በኮቪዲ-19 ምክንያት ለ8 ወር ተቋርጦ የነበረው ትምህርት በ2013 ትምህርት ዘመን ዘግይቶ በመጀመሩ ሌሎች ተማሪዎች ከ4 ወራት በፊት የተመረቁ ቢሆንም የሕክምና ተማሪዎች የተግባር ትምህርቱን በተገቢው መንገድ ተከታትለው መጨረስ ስለሚገባቸው የሚመረቁበት ጊዜ በ4 ወራት መዘግየቱን ፕሬዝዳንቱ ጠቁመዋል፡፡
በዩኒቨርሲቲው የጤና ሳይንስ ኮሌጅ ቺፍ ኤክስክዩቲቪ ዳይሬክቴር ዶ/ር አንተነህ ጋዲሳ በበኩላቸው ዩኒቨርሲቲው የምርምር ዩኒቨርሲቲ እንዲሆን በፌደራል መንግስት መወሰኑን ተከትሎ ለድህረ ምረቃ ፕሮግራሞች ከፍተና ትኩረት በመስጠት አሁን በኮሌጁ የሚሰጡ የ2ኛ ዲግሪ ፕሮግራሞችን ወደ 15 እነዲሁም የሕክምና ስፔሻሊቲ ፕሮግራሞችን ወደ 8 ማሳደጋቸውን አስረድተዋል፡፡ ዶ/ር አንተነህ አክለውም የሥርዓተ ትምህርት ቀረጻና ግምገማቸው ተጠናቆ በዩኒቨርሲቲው ሴኔት የፀደቀ ሁለት አዳዲስ የሕክምና ስፔሻሊቲና ሁሌት የማስቴርስ ዲግሪ ፕሮግራሞች ከሚቀጥለው የትምህርት ዘመን ጀምሮ ተማሪዎችን በተጨማሪነት ለመቀበል መዘጋጀታቸወን አብራርተዋል፡፡
በምረቃ ፕሮግራሙ ላይ የሲዳማ ክልል ጤና ቢሮ ኃላፊ ዶ/ር ሠላማዊት መንገሻን ጨምሮ የተለያዩ የሥራ ኃላፊዎችና የዩኒቨርሲቲው የበላይ አመራሮች ተሳትፈዋል፡፡