በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የአካዳሚክ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት በዩኒቨርሲቲው አዲስ ለተቀጠሩ መምህራን በማስተማር ክህሎት ላይ ከህዳር 15-19 ቀን 2014 ዓ.ም ድረስ ለአምስት ቀናት የሚቆይ ስልጠና በዋናው ግቢ መስጠት ጀምሯል፡፡
የአካዳሚክ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ደይሬክተር ዶ/ር ዘለቀ አርፈጮ እንደገለጹት ይህ ስልጠና ወደ ኒቨርሲቲያችን በ2013ዓ.ም ሁለተኛ ሴሚስተር ላይ በቅጥር እና በዝውውር ለመጣችሁ እና በሁሉም ኮሌጆችና ትምህርት ክፍሎች ለምትገኙ መምህራን የተዘጋጀ ነው ብለዋል፡፡ ዶ/ር ዘለቀ ቀጥለውም ስልጠናው ጠቃሚ መሆኑ ታምኖበት ትልቅ ትኩረት የተሰጠው በመሆኑ ሰልጣኞች በአግባቡ እንዲከታተሉና ተሳታፊ እንዲሆኖ ያሳሰቡ ሲሆን የዚህን መሰል ስልጠና መውሰድ ክህሎታችሁን ከማዳበሩም በተጨማሪ ወደፊት የተለያዩ የትምህርት ዕድልና ኃላፊነት ውድድሮች ላይ ይጠቅማችኃል ብለዋል፡፡
የትምህርት ኮሌጅ ዲን የሆኑት ዶ/ር አብርሃም ቱሉ በስልጠናው መክፈቻ ላይ በበኩላቸው እንደተናገሩት በመማር ማስተማሩ ሂደት እንደመምህር ክፍል ከመግባቱ በፊት ሊታጠቃቸው የሚገባቸው ትጥቅና ክህሎት የሚያስፈልጉት ሲሆን እነዚህም ዝግጁነት፣ ቁርጠኝነት፣ መሰጠት፣ አካታች መሆን፣ሙያዊ ስነምግባር መላበስ፣ አቅጣጫ ቀያሽ መሆን፣ ጊዜን በአግባቡ አመጣጥኖ መጠቀም የመሳሰሉት ይጠቀሱበታል ብለዋል፡፡ ዶ/ር አብርሃም አክለውም ለተከታታይ አምስት ቀናት በሚሰጠው ስልጠና ላይም ሰልጣኞች በመጠየቅ፣ በመሳተፍ እና የገጠማችሁን ተግዳሮትና መልካም አጋጣሚዎች እንደምሳሌ በማንሳት የሚጠበቅባችሁን እንደትወጡ አደራ እላለሁ ብለዋል፡፡