የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ከውጭ ጉዳይ ሚኒስተር ጋር በመተባበር “ሁሉም የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ማህበረሰብ እንደ አንድ ዜጋ ለሀገሩ ዲፕሎማት ነው“ በሚል መሪ ቃል በህዳር 10/2014ዓ.ም በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የፐብሊክ ዲፕሎማሲ ማዕከል ተቋቋመ፡፡
የዕለቱ የክብር እንግዳ ክቡር አምባሳደር ዲና ሙፍቲ የውጭ ጉዳይ ሚኒስተር ቃል አቀባይ የዲፕሎማሲ ማዕከሉ በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ መቋቋሙ በህዳሴ ግድባችን ዙሪያ፣ በሰሜኑ የሀገራችን ክፍል የተከፈተብንን ዘመቻ በማስመልከት እና የምዕራብያኑን የሀሰት የሚዲያ ፕሮፓጋንዳ ለመመከት እና ለመቋቋም ለሀገራችን ዲጂታል ዲፕሎማሲ ሚናው የጎላ መሆኑን ገልጸው ሚኒስተር መስሪያ ቤቱ ማዕከሉ ከአቻ ተቋማት እና የውጭ ጉዳይ ሚኒስተር ጋር በጋራ የሚሰራበትን የአሰራር ስርዓት እንደሚያመቻች እና ተገቢውን ድጋፍ እንደሚያደርግ ተናግረዋል፡፡
የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ዶ/ር አያኖ በራሶ በበኩላቸው እንደተናገሩት የማዕከሉ መቋቋም ለምሁራኖቻችን የፖሊሲ ሃሳብ ለማመንጨት ምቹ ሁኔታን የሚፈጥር እና ተማሪዎችም ስለሀገራቸው መልካም አጋጣሚና ስጋቶች የሚወያዩበት ይሆናል ብለዋል፡፡
የማዕከሉም ዋና ዓላማ ለብሔራዊ ጥቅም የሚሟገቱ ምሁራንን እና ተማሪዎችን ማፍራት፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማትን ጠንካራ ዲፕሎማቶች ማፍለቂያ ማድረግ፣ የከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ተማሪዎችን በብሔራዊ ጉዳዮች ላይ የበለጠ እንዲቀራረቡ ማድረግ መሆኑን የተገለጸ ሲሆን በፕሮግራሙም የአባይ ልጆች በሚል የተዘጋጀ መተግበሪያ ለምሁራኑ ቀርቦ በቀጣይም የማዕከሉ እና የአባላቱ የአደረጃጀት ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ ለማወቅ ተችሏል፡፡