አካዳሚክ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ከፍሬሽማን ፕሮግራም ማስተባበሪያ ቢሮ ጋር በመተባበር በ2013 ዓ.ም ወደ ዩኒቨርሲቲው ለተቀላቀሉ ተማሪዎች ስልጠና ሰጠ
በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ አካዳሚክ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ከፍሬሽማን ፕሮግራም ማስተባበሪያ ቢሮ ተባብሮ ለአዲስ ተማሪዎች በአዲሱ የተማሪዎች ዲሲፕሊን መመሪያ ላይ ህዳር 4 እና 5 ቀን 2014 ዓ.ም ስልጠና ሰጥቷል፡፡ በስልጠና ወቅት በቦታው የተገኙት የአካዳሚክ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ዘለቀ አርፊጮ የመክፈቻ ንግግር ሲያደርጉ ከአዲስ ገቢ ተማሪዎች መካከል 113 የሚሆኑት በዲሲፕሊን ግድፈት ምክንያት የተባረሩ መሆናቸውን ገልጸዋል። በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት ሚኒስተር ወይም MoSHE የተዘጋጀው አዲሱ የዲሲፕሊን መመሪያ ቀደም ሲል ከነበረው የዲሲፕሊን መመሪያ ጋር ሲነፃፀር ጠንካራ በመሆኑ ሁሉም ተማሪዎች ግንዛቤ እንዲጨብጡ ታስቦ የተዘጋጀ ስልጠና ነው ብለዋል። ዳይሪክተሩ ንግግራቸውን ሲቀጥሉ ሰልጠናውን እየወሰዱ ያሉት አዳዲስ ተማሪዎች እንደ መሆናቸው መጠን በዩኒቨርስቲ ቆይታቸው መብትና ግዴታቸውን አውቀው የዲሲፕሊን መመሪያ በሚፈቅደው መሰረት መንቀሳቀስ አንደሚገባቸውና መመሪያውን ተላልፎ የተገኙ ተማሪዎች የዲሲፕሊን ቅጣት እንደሚጠብቃቸው ተናግረዋል።
የገቨርናንስ ትምህርት ቤት ኃላፊው አቶ ዳኜ ጥላሁን በበኩላቸው ተማሪዎቻችን ከሀገራችን ከተለያዩ ክልልሎች የመጡና የየራሳቸው ባህል ካሏቸው ማህበረሰቦች የተወጣጡ ስለሆኑ ከተቋሙ ባህልና ከአዲስ የዲሲፕሊን መመሪያ ጋር እንዲተዋወቁ ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን ተናግረዋል። ኃላፊው በርካታ ተማሪዎች ግንዛቤ ከማጣት የተነሳ መመሪያ በመጣስ ችግር ውስጥ መግባታቸውን አውስተው የዚህ አይነት ሁኔታ እንዳይደገም የመጡበትን ዋና አላማ ሳይዘነጉ በትምህርታቸው ስኬታማ ለመሆን ጊዜአቸውን በአግባቡ መጠቀም እንዳለባቸው እና የተሻለ ውጤት ለማስመዝገብ
መጣር እንዳለባቸው አሳስበዋል።
በመጨረሻም በዲሲፕሊን መመሪያ ላይ ስልጠና ከሰጡት መካከል አንዱ የሆኑት የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ መምህር እና ተመራማሪው ዶ/ር ከበደ ተ/ሚካኤል ስልጠና በሰጡበት ወቅት እንደተናገሩት ተማሪዎቹ ከዚህ ስልጠና
የሚያገኙአቸውን ክህሎት በአግባቡ በመጠቀም በግቢ ቆይታቸው የተሻለ ስነምግባር ያው ተማሪ ሆነው መውጣት እንደሚጠበቅባቸው ጠቁመዋል።