ሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ የአንደኛ ዓመት ሁለተኛ ሴምስቴር ተማሪዎችን ተቀብሎ ምዝገባ እያካሄደ ይገኛል።
የሬጅስትራር እና አሉሚኒ ጉዳዮች ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር ዶ/ር ዘሪሁን ክንፈ እንደተናገሩት የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በዘንድሮዉ የትምህርት ዘመን 3405 የሚሆኑ የአንደኛ አመት ሁለተኛ ሴሚስቴር የተማሪዎች ምዝገባ እየተካሄደ እንደሆነ ተናግረዋል፡፡ ተማሪዎቹን ተቀብሎ የሚያስተምረዉ በተለያዩ የትምህርት ዘርፎች ማለትም በሜዲሲን፣ በቬተርናሪ፣ በሕግና በፋርማሲ ተማሪዎቹ በመጀመሪያ ሴሚስቴር በነበራቸው ውጤትና 12ኛ ክፍል ሲፈተኑ በነበራቸዉ ውጤት እንደተመደቡ ዳይሬክተሩ አያይዘው ተናግረዋል፡፡
ኮቪድ-19 ከተከሰተ ጊዜ ጀምሮ የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ተማሪዎቸን በተለያዩ የትምህርት ዝግጅቶች እየተቀበለ በማስተማር ላይ የሚገኝ ሲሆን አሁን ደግሞ ከ2ኛ ዓመት ጀምሮ ያሉትን ተማሪዎች ከ2014 ጀምሮ በትክክለኛው የትምህርት መርሃ ግብርና ወደ ትክክለኛው የትምህርት ርዝማኔ እንደተመለሱ ዶ/ር ዘሪሁን ክንፈ የገለጹ ሲሆን የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ በአጠቃላይ የመጀመሪያ ዓመት ተማሪዎችን ጨምሮ ከ34 ሺ ተማሪዎች በላይ በመደበኛ፣ በዕረፍት ቀናት፣ በማታና በክረምት እንዲሁም በመጀመሪያ፣ በሁለተኛና በሶስተኛ ዲግሪ ተቀብሎ እንደሚያስተምር አስረድተዋል፡፡
አክለውም ነባር ተማሪዎች ከባለፈው ሐሙስ ጀምሮ ትምህርታቸውን መከታተል መጀመራቸውን አንስተዉ አሁን የሚገቡ ተማሪዎች የምዝገባ ሂደት ከፈጸሙ በኋላ ከቀን 18/02/2014 ጀምሮ ወደትምህርታቸው እንደሚገቡና ተማሪዎቹም በትምህርት ገበታቸው ላይ ተገኝተው ትምህርታቸውን እንዲከታተሉ ዳይሬከተሩ አሳስበዋል፡፡