በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ማህበራዊ ሳይንስና ስነ-ሰብ ኮሌጅ በ“ህይወት ክህሎት” እና “የመተው ጥበብ” ርዕሰ ጉዳዮች ላይ በኮሌጁ ምሁራን አቅራቢነት ለሀላፊዎች፣ ለመምህራንና ለሠራተኞች የማነቃቂያ ስልጠና መስከረም 19 ቀን 2014 ዓ.ም ሰጥቷል፡፡
የኮሌጁ ዲን ዶ/ር ዳኜ ሽብሩ የዕለቱን መክፋቻ ንግግር ሲያደርጉ በኮሌጁ መጠነ ሰፊ ስራዎች እየተሰራ እንደሚገኝ ገልጸው ለአብነት የጋዜጠኝነትና ኮሚዩኒኬሽን ትምህርት ክፍል የተለያዩ የኦን ላይን ፕሮግራሞችን በማዘጋጀት አስተማሪ ተግባራትን በመፈጸም ላይ እንዳለ ተናግረዋል፡፡
በዩኒቨርሲቲው የእንግሊዝኛ ቋንቋና ሥነጽሑፍ ትምህርት ክፍል መምህር የሆኑት ዶ/ር ተስፋይ ሰሎሞን በመተው ጥበብ ላይ ስልጠናውን የሰጡ ሲሆን በጽንሰ ሀሳቡ ዙሪያ በጥልቀት በማንሳት ሙያዊ ሀሳባቸውን ለሰልጣኞቹ አጋርተዋል፡፡ መተው ሲባል ጎጂዎችን መተው ላይ ያተኮሩ ነጥቦችን በማንሳት ፍርሃትን፣ አስቸጋሪ ሰዎችን፣ ልማዶችን እና ማጣትን በአግባቡ መያዝ የሚሉትን ሳይንሳዊ ምክረ ሀሳቦችን በሰፊው ዳሰዋል ዶ/ር ተስፋይ በስልጠናቸው፡፡
ለላኛው በኮሌጁ የሳይኮሎጂ ትምህርት ክፍል መምህር የሆኑት እጩ ዶ/ር ሀብታሙ ካሣ የተለያዩ ስና ልቦናዊ ምክር የያዙ የሕይወት ክህሎት ጉዳዮችን በማንሳት ከጎጂ ጭንቀት ለማምለጥ ጤናማውን ጭንቀት እንዴት ወደ ስኬት መቀየር እንደሚቻል በጥልቀት ዳሰዋል፡፡
በዕለቱ ከተለያዩ የስራ ክፍል ሀላፊዎች እና ከኮሌጁ ማህበረሰብ የተጋበዙ ወደ 100 የሚጠጉ ተሳታፊዎች ስልጠናውን በልዩ ትኩረት ከመሳተፋቸው ባሻገር መንፈሳቸውን ያነቃቃና የአዕምሮን እረፍት የሰጣቸው ስልጠና መሆኑን በመግለጽ እንዲህ ዓይነት ስልጠና በየመንፈቁ ቢዘጋጅ እና ብዙዎች የሚሳተፉበት ቢሆን መልካም እንደሆነ ሀሳባቸውን ሰንዝረዋል፡፡ በመጨረሻም የኮሌጁ ዲን ዶ/ር ዳኜ በስራ ብዛት የተያዘ አዕምሮና መንፈስ ሳይታደስ ስኬታማ መሆን እንደማይቻል ጠቅሰው እንደኮሌጃችን በመሳሰሉ ርዕሰ ጉዳዮች ላይ የሚያተኩሩ ስልጠናዎችንና ውይይቶችን ለተማሪዎችና መምህራን ማዘጋጀታቸውን እንደሚቀጥሉ ቃል ገብተዋል፡፡