በሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ስትራቴጂክ ዕቅድ ቁልፍ የውጤት አመላካቾች ላይ ግንዛቤ ለመፍጠር የውይይት መድረክ ተዘጋጀ።
መድረኩ የተዘጋጀው በግብርና ኮሌጅ ግቢ ሲሆን የሀዋሳ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዝዳንት ጽ/ቤት ሀላፊ አቶ አየለ አዳቶ በመክፈቻ ንግግራቸው በምርምር ዩኒቨርሲቲዎች ተርታ በመፈረጃችን ምክንያት ከበፊቱ በተሻለ የላቀ አፈጻጸም ደረጃ ላይ እንድንደርስ ተሻሽለው በቀረቡ ግቦችና ቁልፍ የውጤት አመላካቾች ላይ በማተኮር በቂ ውይይት ለማድረግ በታሰበው መሠረት ፕላንና ተቋማዊ ለውጥ ዳይሬክቶሬት በሚያቀርበው የመነሻ ሀሳቦች ላይ በቂ ግንዛቤ ተይዞ መድረኩ እንዲያበቃ አሳስበዋል፡፡ የፕላንና ተቋማዊ ለውጥ ዳይሬክቶሬት ዳይሬክተር አቶ ሙሉጌታ ቡርቃ እንደገለጹትም በዩኒቨርሲቲው ራዕይና ተልዕኮ ላይ መጠነኛ ማሻሻዎች የተደረጉ ሲሆን ዩኒቨርሲቲያችን አሁን ለማወቅ እንደተቻለው ከአሥራ አንዱ የምሥራቅ አፍሪካ ሀገራት ከ17-23 ደረጃን ይዛ የምትገኝ ቢሆንም በቀጣይ 10 ዓመታት ውስጥ ከ1-10 ባሉ ደረጃዎች ውስጥ የምትገባበት ራዕይ ተይዞ ለመሥራት መታቀዱን ገልጸዋል፡፡ በዩኒቨርሲቲው የሚዘጋጅ ተቋማዊ ዕቅድና ሪፖርት ከዩኒቨርሲቲው ራዕይና ተልዕኮ ጋር ፍጹም የተጣጣሙ መሆን ስላለባቸው የተሻሻሉ ጉዳዮች ላይ ውይይት አስፈልጓል፡፡ በዚህም መሠረት ዩኒቨርሲቲ አቀፍ ግቦችን እና ቁልፍ የአፈጻጸም አመላካቾችን ለይቶ የአፈጻጸም አቅምን መለካት ተገቢ በመሆኑ ሁሉም አካላት ግንዛቤ መጨበጥ እንዳለባቸው ዳይሬክተሩ አቶ ሙሉጌታ ቡርቃ ለተሳታፊዎቹ በአጽንዖት ተናግረዋል፡፡ በውይይቱ የተለያዩ ጥያቄዎች የተነሱ ሲሆን በመድረኩ ላይ የተሳተፉ የዩኒቨርሲቲ አመራር አካላት ሰፊ ሀሳብ በማንሸራሸር ጥልቀት ያለውን ውይይት አካሂደዋል፡፡